የፓቶጵያ ፍቅር
5/5
()
About this ebook
ተወደደም ተጠላም በአዲሱ የዓለም ስርዓት ፣ አንዱ የበላይ ሌላው የበታች ፤ የሚኾነው በመረጃ ነው። ለራሳቸው ለማወቅ መረጃ ይሰበሰባል፣ ይተነተናል። እኛን ላለማሳወቅ ይደመሰሳል፣ ይበረዛል። ለማጋጨት ይመረታል፣ ይሰራጫል። መረጃ መስሪያም መሳሪያም ነው። ማንም ፈቅዶ የበታች ፤ ዝም ብሎም የበላይ አይኮንም። መስሪያም መሳሪያም ተጠቅሞ እንጂ።
መረጃ ይፈለጋልም ፣ አይፈለግምም። መረጃ ይጠቅማልም ፣ ይጎዳልም። መረጃ ማወቅ ነው፣ መደንቆርም ነው።
መቼ፣ የቱ እና ምንነቱ ሲታወቅና ፤ ዓቅሙ ካለ ብቻ መረጃ ያስፈልጋል፣ ይጠቅማል፣ እውቀት ስለሆነ ፤ መሰብሰብ፣ መተንተን እና በተግባር መተርጎም አለበት። የዳይስቶጵያ ሴራ በመረጃ ምርት እና ስርጭት ላይ የተመሰረተ ፓቶጵያ እንዳታቆጠቁጥ የሚያደርግ የጥፋት ሴራ ነው።
Hailu Worku Obsse
Hailu Worku Obsse is an Ethiopian writer, researcher and software developer who is currently pursuing his PhD in Optimization Engineering at Ecriyes University in Turkey. He has authored more than 12 books, published many research articles and contributed much to the development of literature
Related to የፓቶጵያ ፍቅር
Related ebooks
ውበት አውሬው እና መጋቢው Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsየነርሱ ኑዛዜ Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsከእናንተም አንዱ ዲያብሎስ ነው Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsአድዋ ከዋዜማሽ እስከ ድል ቀንሽ Rating: 1 out of 5 stars1/5እንደ እባብ ብልህ መሆን ማለት ምን ማለት ነው Rating: 5 out of 5 stars5/5ምርቃት እና እርግማን Rating: 5 out of 5 stars5/5ዳግም መወለድ ብሎም ገሃነምን ማስወገድ Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsሌሎች Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsየመጋቢነት አገልግሎትህን ወደ ላቀ ደረጃ አሳድግ Rating: 5 out of 5 stars5/5የኩራዙ ተፅኖ Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsበዘፍጥረት ላይ የተሰጡ ስብከቶች (VI) - የሰውን ዘር ከጥፋት የሚያድን የወንጌል ምስክር ሁኑ (Amharic 54) Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsየጥንቱ ወንጌል ጥበብ (Amharic53) Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsአደገኞች ልጆች Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsበሥዕል የተደገፈ የዕባዳዎች አፈጻጸም ፍቅህ Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsበውኑ በውሃውና በመንፈሱ ዳግም ተወልዳችኋልን? Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsበዕብራውያን ላይ የተሰጡ ስብከቶች (I) - እምነታችሁን እንዴት ማጠንከር ትችላላችሁ? Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsላይኮስ ተኢው ስው እር አንልግኤት Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsወደኋላ ማፈግፈግ Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsትልቅ ቤተክርስቲያን Rating: 2 out of 5 stars2/5ትእቢተኞች Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsመንፈሳዊ አደጋዎች Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsአስመሳዮቹ Rating: 3 out of 5 stars3/5በየቀኑ ከእግዚአብሔር ጋር ውጤታማ የጥሞና ጊዜ ሊኖርህ ይችላል Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsየአገልግሎትህን እስከ መጨረሻው እንዴት ማድረስ ትችላለህ Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsየተጠሩ ብዙዎች ናቸው Rating: 5 out of 5 stars5/5ልጄ ሆይ ትችያለሽ Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsየሚከሱህ ሰዎች Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsዛፉ እና አገልግሎትህ Rating: 0 out of 5 stars0 ratingsጣፋጭ የመንፈስ ቅዱስ ተፅዕኖዎች Rating: 4 out of 5 stars4/5ዝንጉዎቹ Rating: 5 out of 5 stars5/5
Related categories
Reviews for የፓቶጵያ ፍቅር
1 rating0 reviews
Book preview
የፓቶጵያ ፍቅር - Hailu Worku Obsse
መታሰቢያነቱ
ሕይወታቸውን ለአገራቸው ደህንነት ሲሉ በገደል በሸንተረሩ ለተሰዉ ጀግኖች እና ለሰፊው ህዝብ።
ልብ ወለድ ታሪክ ገፅ
በመጀመሪያ
ዮናታን ያኔ ከአገር ሲወጣ ሁሉም ነገር ሰላም ነበር። እንደዛሬው ዛሬ ፣ በአገሪቷ ውስጥ ፤ ሁሉም ነገር ግልብጥብጡ ወጥቶ ፤ መኖር እንደ ምጥ አስጨናቂ አልነበረም። ያኔ ሳሩ ቅጠሉ ሁሉ፣ በአንዳች ክፉ ነገር ተመርዞ ፤ የሚተነፈሰው አየር ሳይቀር ሞት ሞት አይሸትም ነበር። ምድሪቱ ክፉኛ ከመጨከኗ የተነሳ ፤ የተዘራውን ማብቀል ትታ የተለኮሰውን ማቀጣጠል ብቻ አልነበረም ሥራዋ። በሁሉም የአገሪቷ መንገዶች ላይ በዓይን የማይታዩ የደም ኬላዎች ተሰርተው ፤ ሰው ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መንቀሳቀስ አይቸገርም። ዛሬ ነገሩ ሁሉ ሰላም አይደለም።
ማንም ያንን ሰላምን ድራሿ ያጠፋት ክፉ ነገር አያውቀውም። ቢያውቀውም ይህን ያህል ይሆናል ብሎ አያምንበትም። ቢያምንበትም እንኳ ለመፍታት አይሞክረውም እንጂ ፤ ምክንያቱስ ለዚህ የሚያበቃ አልነበረም። ህዝቡን እሳትና ጭድ አድርጎ ፣ አንዱ በአንዱ ላይ ያስነሳው ፣ ዜጋው ሁሉ ወንድሙ ገዳይ ጀግና ያደረገው ፣ አፍ እንጂ ጆሮ ያሳጣው ፣ ዓላማ አሳጥቶ ፣ ባለ ኢላማ ብቻ ያደረገው ምክንያት ፤ ለዚህ የሚያበቃ አልነበረም።
ቅጥ ባጣ የሞት ግጥምያ ፣ ዳኛ በሌለበት ዝግ ሜዳ ፤ ሁሉም የሞት ግብ አግቢ ሆኗል። መበላላቱ ጦፎ ፤ ጠዋት የበላው ከሰዓት በተራው ይበላል። ገዳዩ ያው ሟቹ ስለሆነ፤ የገዳይና የሟች ቁጥሩ አንድ ነው። ማስተዋል ጭራሽኑ ጓዙን ጠቅልሎ እንጠሮጦስ ገባና፣ ድንቁርና ራሱን አድሶ ፣ ከሊቁ እስከ ደቂቁ ሳይለያይ ፤ በሁሉም ላይ ተንሰራፋ። ማንም ማስተዋል አይፈልግም። ዮናታን ግን፤ አገሩ ለምን እንዲህ እንደሆነ ሳይፈልገው አወቆታል – የዳይስቶጵያ ሴራ ነው። ይህ አገሪቷን እና ህዝቦቿን በጥቂት አመታት ሊያጠፋ የተጠነሰሰን ሴራ በአጋጣሚ አወቀውና ሳይፈልገው ወደ ትግል ገባ። ሴራውን የማስቆም ትግል። ብዙ ታገለ፣ ዋጋ አስከፈለው። ሴራው፣ ትግሉ እና ፍፃሜው በዚህ መልክ ተተርኳል።
ልብ ወለድ ታሪክ ገፅ
––––––––
አሀዱ
ስፍን ድኅር ነገር ለውእቱ
- ፩ -
ተወደደም ተጠላም በአዲሱ የዓለም ስርዓት ፣ አንዱ የበላይ ሌላው የበታች ፤ የሚኾነው በመረጃ ነው። ለራሳቸው ለማወቅ መረጃ ይሰበሰባል፣ ይተነተናል። እኛን ላለማሳወቅ ይደመሰሳል፣ ይበረዛል። ለማጋጨት ይመረታል፣ ይሰራጫል። መረጃ መስሪያም መሳሪያም ነው። ማንም ፈቅዶ የበታች ፤ ዝም ብሎም የበላይ አይኮንም። መስሪያም መሳሪያም ተጠቅሞ እንጂ።
መረጃ ይፈለጋልም ፣ አይፈለግምም። መረጃ ይጠቅማልም ፣ ይጎዳልም። መረጃ ማወቅ ነው፣ መደንቆርም ነው።
መቼ፣ የቱ እና ምንነቱ ሲታወቅና ፤ ዓቅሙ ካለ ብቻ መረጃ ያስፈልጋል፣ ይጠቅማል፣ እውቀት ስለሆነ ፤ መሰብሰብ፣ መተንተን እና በተግባር መተርጎም አለበት። የዳይስቶጵያ ሴራ በመረጃ ምርት እና ስርጭት ላይ የተመሰረተ ፓቶጵያ እንዳታቆጠቁጥ የሚያደርግ የጥፋት ሴራ ነው።
ምዕራፍ አንድ
ዮናታን
ቀኑ ዕልተ ሐሙስ፣ ቦታው ጆርጂያ ፣ አትላንታ ፣ ሚድታውን በሚገኘው የሳይበር ሳን ዋናው ቢሮ ነው። ትውልደ ኢትዮጵያ፣ የቀድሞ ስሟ ማሮያማዊት የሆነችው፤ ወ/ሮ ማሪያ ዴቪድ ባሏ አቶ ዴቪድ፥ ከአንዲት ወጣት ጋር ሲወሰልት የሚያሳዩ ምስሎችን በፕሮጀክተር እያየች ነው። ከጎኗ የግል የስለላ ኦፊሰር ተቀምጣል። ኦፊሰሩ ሥራው በትዳራቸው ላይ የሚወሰልቱ ወስላቶችን እየሰለለ ማስረጃና መረጃ መሰብሰብ ነው። ሰዎች በትዳራቸው ላይ የሚወሰልቱት ፤ ከትዳራቸው ካገኙት ይልቅ ባጡት ነገር ስለሚያቶኩር ነው ብሎም ያምናል።
"እይልኝ ... ይህ ቅሌታም! እንዴት አባቱ እንደሚስማት! እስቲ አሁን ከኔ ምን አንሶት ነው ይህችን ፉንጓ የሚያማግጠው ?! ወይኔ ዴቪድ ተጫወትክብኝ! እኔ ማሪያ አይደለሁም ታያለህ ካልሰራሁልህ ..." ማሪያ ባሏ ዴቪድ ሌላ ሴት ሲያማግጥ የሚያሳይ ፎቶግራፍ እየተመለከተች በቅናት ትበግናለች። ኦፊሰሩም ፎቶግራፎችን አንድ በአንድ እያሳየ ስለ ሁኔታው ያስረዳታል። ዴቪድ ያችን ወጣት ሴት ፣ ለብዙ ጊዜ ሲማግጥ እንደነበር አወቀች። ምስሎቹ በፕሮጀክተር ጎልተው ግድግዳውን ሞልቶት ሲታይ ፤ የተመልካችን ስሜት በጣም ይረብሻሉ። በተለይ ደግሞ ለትዳር አጋር ፤ የቅናት ስሜት የሚቀሰቅሱ ናቸው። ማሪያ ባሏን ዴቪድን ለማሰለል ፤ ከሃያ ሺህ ዶላር ያላነሰ አውጥታለች።
ይህች መተታም ፉንጋ ምን አባቷ ብታስቀምሰው ነው ፤ ይህ ቅሌታም እንዲህ የሙጭኝ ብሎ የቀረው ?!
ብላ ትለፈልፍ ነበር። በእርግጥ ማሪያ እንደምትሰድባት ፤ ወጣቷ ሴት ፉንጋ አልነበረችም። ማሪያ ፎቶዎችን እያየች በሄደች ቁጥር ቅናቷ እየጨመረ ሄዶ ፤ ሊያቅለሸልሻት ምንም አልቀረውም። ለበቀል ያላትም ስሜት እጅግ በመጨመሩ ፤ በቀሉን በቅርቡ መጀመር እንዳለባት በልቧ ወሰነች። በድንገት ግን አናቷን የተመታች ያህል ፤ ክው ያደረጋትን ፎቶ ስክሪኑ ላይ ገጭ ብሎ አየች። ከወንበሯ ተስፈንጥራ ተነሳች እና ኦፊሰሩም ትኩር ብላ አየችው ፤ እርሱም ባየው ያለተፈለገ ፎቶግራፍ እጅግ ደንግጣል።
ባሌን ሰልሉልኝ አልኩኝ እንጂ ፣ እኔን ሰሉልኝ መች አልኩኝ? ይህ ምን ዓይነት እብደት ነው ?
ብላ ጮኸች። ማሪያ ስትበሰጫጭ ድምፃ እጅግ ከፍ ያለ ነበር። ድምፃ ካለችበት ክፍል አልፎ ፤ ሌሎች ክፍሎች ድረስ ይሰማል። የሰሙ ሁሉ በሁኔታዋ እጅግ ተደናገጡ።
እመቤቴ እባኮትን ይረጋጉ። ይህ ፎቶ በስህተት ነው የተቀላቀለው። የእርስዎን ትዕዛዝ ተቀብለን፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርጥ መረጃዎችን ሰብስበናል።
እያለ ኦፊሰር የተሰበሰበውን ፎቶዎችን ማሳየቱን ሊቀጥል ሞከረ። ሴትዮዋ ግን በጭራሽ አልረጋጋ ብላ ከፍተኛ ሁከት ፈጠረች። ያየችው ፎቶ የራሷን የወሲብ ቅጥፈት የሚያሳይ ነበር። ባለቤቷን ሸውዳ ፤ ከሌላ ወንድ ጋር ስትማግጥ በግልፅ የሚያሳይ ፎቶ። ተቁነጠነጠች። ንዴቷ መቋቋም አቃታት። ከንፈሮቿ ይንቀጠቀጣሉ፣ አይኖቿ ተበልቅጠው ፈጠጡ።
ፍርደ ገምድል በመሆኗ እና ልቧ እውነታውን አልቀበልም በማለት እንጂ ፤ መማገጡስ በእርሷ ይብሳል። ባሏ በሥራ ተጠምዶ መፈናፈኛ ባጣ ጊዜ ውጪ ውጪ ማለቱን የጀመረችው እርሷ ነበረች። ለዚያውም ከቅርብ ጓደኛው ጋር። ባለቤቷ ዴቪድ ሚስትህ አልሰማህ ካለችህ ፤ ሌላ ሴት ማዋራት ስትጀምር ትሰማሀለች።
ብሎ ነበር ያችን ወጣቷ ጋር ጎራ ማለት የጀመረው።
ማሪያ ለሳይበር ሳን ባሏን እንዲሰልሉላት ኮንትራት የሰጠችው ፤ ባሏ ከሴቶች ጋር እየማገጠ ነው የሚለው ወሬ በመወራቱ ነበር። ከዚያም ከስለላው በሚገኘው መረጃና ማስረጃም ተጠቅማ ፤ ባሏን ፍርድ ቤት ለመገተርና ፣ ለበቀል ነበር።
ሳይበር ሳን ከሌሎች በድፍን ጆርጂያ ካሉ የግል ስለላ ድርጅቶች አንደኛ ነው። ማንም ሰው የትዳር አጋሩን ከጠረጠረ ፤ ሳይበር ሳን መረጃ አነፍንፎ ይሰጠዋል። መረጃ በማፈላለጉና በማግኘቱ ሳይበር ሳንን የሚያክል የለም። ይህ እውነታ ግን ለሚስኪኗ ማሪያ አልሰራም ... በሰፈረችው ቁና ... ሆኖባት አናዷታል።
ለካስ ዴቪድ አውቆ እንዳላወቀ ቢያደፍጥም ፤ ተመሳሳይ ቅሬታ ነበረበት እና ፤ ሚስቱን ለማሰለል ኮንትራቱን ለሳይበር ሳን ሰጥቷል። ታዲያ በስም መገጣጠም ይሁን ፣ በሰይጣን አሳሳችነት ፤ ከበርካታ ፎቶግራፎች መሀል አንዲት ፎቶ አመለጠችና፤ ለማሪያ በተዘጋጀው ፎልደር ውስጥ ተቀላቀለች። ኦፊሰሩም ስለተገኙት መረጃዎች እያስረዳ ሳለ ፤ በድንገት ያችን ፎቶ በትልቁ ስክሪን ግድግዳውን ሞልታው ታየች። ማሪያ እየተሰለለች እንደነበር ገና ዛሬ አወቀች። ባሏ እርሷ እንዳሰለለችው ሁሉ እርሱም አሰልሏታል። እርሷ ባሏ ሲባልግ እንደነበር እንደምታውቀው ሁሉ እርሱም ሚስቱ ስትባልግ እንደነበረች ያውቀዋል ማለት ነው።
ሳይበር ሳን ውስጥ ስለላ በከፍተኛ ቁጥጥር ነው የሚሰራው። ማንም የማንንም መረጃ ፤ ምንም ያህል ቢከፍል ማጥፋት አያችልም። ቢቻል ኖሮ ማሪያ የከፈለች ከፍላ ፣ እነዛን የእርሷን ቅሌት የሚያሳዩ ምስሎች ታስጠፋቸው ነበር። ገርሟታል፣ ቅሌቷን በሌላ ሰው ቅሌት ፍለጋ ውስጥ አየችው። ቅሌቷን አይታ እንዳላየች ዝም ማለት አትችልም። ሌላው ቢቀር ያንን እነርሱ ሰፈር የሚኖረው የሳይበር ሰን ተቀጣሪ የሆነውን ዮናታን ደሞዝን የከፈለች ከፍላ እንዲረዳት መለመን አለባት።
የእነ ማሪያ መኖሪያ ቤት ፣ ከዮናታን ደሞዝ መኖሪያ ቤት ብዙም አይራራቅም። ዮናታን ደሞዝ የሚባለው ትውልደ ኢትዮጵያዊ ሳይበር ሳን ውስጥ በመረጃ ቋት እና መረብ ደህንነት ላይ የሚሰራ ባለሙያ ነው። ማሪያ ዮናታንን ሳይበር ሳን እንደሚሰራ ፤ ከአንድም ሁለት ጊዜ ስትገባና ስትወጣ አይታዋለች። አናግራው ግን አታውቅም። እርሱም አናግሯት አያውቅም። ማሪያ ባየችው ፎት በመደንገጧ ስትጮህ ግን ሰምቷታል። ምን ሆና ጮኸች ብሎ ሲጠይቅም ፤ በወሬ ወሬ ሚስጥሯን ሰምቷል።
* * *
እውነት ባይሆንም ቅሉ፣ የሰው ልጆች የኑሮን ጣዕም አጥተን ፣ አለመኖር የምንመርጠው ፤ በኑሮ የጎደለን ነገር የነፍስ ጥያቄ ከሆነ ነው ይባላል። ይህ ሐቅ ለሁሉም ሰው ባይታሰብም፤ ለአንዳንዶች ግን እውነት ነው። አንዳንዱ ከበላና ከጠጣ ስለ ሌላው ጉዳዩ አይደለም። አንዳንዱ ደግም መኖር የሚባለው ያሻህን ፈልገህ ስታገኝ እና ሲተርፍህ ነው ይላል። ለዮናታን ደሞዝ ግን ኑሮ ይህ ብቻም አይደለም። ዮናታን እንደሚለው መኖር ማለት ጊዜና ገንዘብ ኖሮህ ፤ ሌሎች ኑሮን ራሷን ሲኖሯት ፤ ምንም ሳይጎልብህ ቆም ብሎ ማየት ሲቻል ነው። ዮናታን እንኳንስ የሌሎች የራሱን ኑሮ ቆሞ ለማየት ሳይችል እንደ እንዝርት ሲዋከብ ይኖራል።
በሳይበር ሳን ተቀጥሮ በመሥራት ፤ እሱ ኑሮ የሚለውን ዓይነት ኑሮ ለመኖር የሚያስችል በቂ ጊዜና ገንዘብ ሳያገኝ እየኖረ ነው። በዚያ ላይ ፤ እናቱንና ወንድሙን መጦር ተጨምሮበት፣ በሳይበር ሳን ተቀጥሮ መሥራት የጀመረው የዛሬ አምስት ዓመት ገደማ ነው። ሳይበር ሳን የተሰማራው በግል የስለላ ሥራ ላይ መሆኑን በሥራው ደስተኛ አይደለም። ሰለላ ብልግና ነው፤ ሰላይ ደግሞ ነፍስ የለውም ብሎ ያስባል። ሳይበር ሳን በጆርጂያ ግዛት፣ በአትላንታ ከተማ፣ በሚድታውን ንዑስ ከተማ ከሚገኘው ዋና መሥሪቤት በተጨማሪ በሌሎች ግዛቶች እና ከተሞችም በርካታ ቢሮዎችም አሉት።
ዮናታን ትምህርቴን የሚመጥን ሥራ አጣሁኝ ብሎ የሚያስበው የመጀመሪያ ዲግሪውን በሶፍትዌር ኢንጂነሪንግ ፣ የማስተርስ ዲግሪውንም ደግሞ በአርተፊሻል ኢንተለጀንስ ፤ ከታዋቂ ዩኒቨርሲቲ በከፍተኛ ውጤት ስለተመረቀ ነበር። ግን ምን ያደርጋል፣ አርቲፊሻል ኢንተለጀንሱ ተማረው እንጂ፤ አልሰራበትም። በተለይ ሁለተኛ ዲግሪውን ሲመረቅ ፣ የመመረቂያ ፅሑፍ ጥናቱን ያደረገው ፤ ጉድ በሚባልለት ሶፍትዌር የሚሰራ ሶፍትዌር በመሥራት ላይ ነበር። የጥናቱን ተግባራዊነት ለማሳየትም ፤ የተለያዩ ኩፓንያዎችን ድህረገፅ ራሱ የሚሰራ ሶፍትዌር ሰርቶ ነበር።
* * *
ማሪያ ቢሮውን እየተራገመች ወጥታ ስትሔድ በድጋሚ ከዮናታን ፊት ለፊት ተያዩ። ከሄደች ጀምሮ ፤ ማሪያ ባሏን ስታሰልል ፤ ባሏም እያሰለላት እንደነበረ ሁሉም እየተሳሳቁ ሲያወሩ፣ ዮናታን ገረመው። የገረመው ደግሞ የማሰለሏ ዓላማ ባሏን ለበቀል እንደነበረ ሲያውቅ ነው። ምነው ማሪያ የምትኖረው በአፍሪካ በሆነና ውሽሞች ያሉት ባል በኖራት ?!
ሲል ተመኘላት።
* * *
ዮናታን ሁሌም እንደሚያደርገው ፤ ዛሬም ከስራ መልስ በዕለተ ሐሙስ ሙዚቃውን ከፍቶ ወደ ቤቱ ይከንፋል። ሐሙስ ሐሙስ የሚያዳምጠው የአማርኛ ዘፈኖችን ነው። ወይ ኑሮ...
የሚለውን የአስቴር ዘፈን እየኮመኮመ ፤ መኪናውን እያበረረ ከሚሰራበት ድርጅት ወደ ቤቱ ይከንፋል።
ምን እንደሚያስከንፈው ባያውቀውም ልቡ ዝም ብሎ ይሮጣል። ሥራ ቦታ ሲሆን ወደ ቤት ፤ ቤት ሲሆን ደግሞ ውጣ ውጣ ይለዋል። አንዳንዴ ቤት ብቻውን ቁጭ ሲል የሚሰራው ያጣና ትካዜ ይወረዋል። ብቸኝነቱ እንደዚህ እንደሚያደርገው ያስብና ፣ ሐበሾች ወደሚበዙባቸው መዝናኛ ቦታዎች ጎራ ይላል። ምን ያደርጋል ፤ እዛም ሲሄድ የሚያዝናናው ነገር ብዙም አያገኝም። ይህንን ሁኔታው ያዩ አንዳንድ ሰዎች ፣ ዮናታን አንዳች የጤና ችግር ይኖርበት ይሆን ሲሉ ይጠራጠራሉ። ዮናታን ከገቢ ማነስና ከብቸኝነት ስሜት ውጪ፤ ምንም ዓይነት የጤና ችግር የለበትም።
የአስቴር ሙዚቃዎችን እየኮመኮመ ለአንድ ሰዓት የሚሆን ነድቶ በዲካልብ ካውንቲ ውስጥ ፣ ዲክተረ በተባለች ከተማ ወደሚገኘው ቤቱ ደረሰ። ቤቱን በብድር ነው የገዛው። ዕዳው ገና ሃያ አምስት ዓመት ይቀረዋል።
ዲክተር ሠላሳ ሺህ የማይበልጥ ነዋሪ ያላት፣ በጋ እና ክረምቷ በውል የማይታወቅ፣ ሰው እንደ መናፍስት ሌሊቱን ሙሉ ሲንቀዋለልባት የምታድር እና በርካታ ሐበሾች የማያዘወትሯት፣ አነስተኛ ከታማ ነች። በሩን ከፍቶ እንደገባ ቴሌቭዥን ከፈተው። ሦስት ሰዎች በኢትዮጵያ ወቅታቂ ሁኔታ ይከራከራሉ። ትንሽ አዳመጣቸው ፤ እንደሰሞኑ ሁሉ የተከራካሪዎቹ ንግግር ስላናደደው ቴሌቭዥኑን ዘግቶ ለመተኛት ወሰነ። ቴሌቪዥኑን ቢዘጋውም የክርክራቸው ሀሳብ ግን ፤ በህሊናው ሳይዘጋ አብሮት መኝታ ክፍል ሄዶ አላስተኛህ አለው። እንዴት ነው የሚያስቡት ?
ሲል ራሱን ጠየቀ ፤ የሚመልስለት አልነበረም።
ኤጭ የዘንድሮ ፖለቲካ እንደ ቫይረስ ነው፣ በቀላሉ ይጋባል።
አለ ሐሳቡ እንዴት ወደ ውስጡ እንደተጋባ በማስተዋል።
ዮናታን ከኢትዮጵያ ከመጣ እንሆ ድፍን አስር አመት ሆኖታል። ቀዝቀዝ ያለውን የአትላንታ አየር ብቸኝነቱን ሆድ እያባሰበት፤ አንዴ እየተከዘ ሌላም ጊዜ እየቆዘመ ኑሮ ብሎ በማይቀበለው አኳሀን እየኖረበት ነው።
* * *
የዮናታን በር ተንኳኳ እና ከፈተው። ያቺ ማሪያ ነች። ወቅቱ ፀሐይ በጊዜ የምትጠልቅበት የፀደይ ወቅት በመሆኑ ፤ ሰዓቱ ገና ቢሆንም ሰፈሩ ጨለምለም ብሏል። ማሪያ ይህንን ደንገዝገዝ ያለውን ሰዓት ጠብቃ ነበር የመጣችው። ግቢ አላትና ገብታ ተቀመጠች። ራሷን አስተዋወቀችና ወደ ጉዳዩ ገባች። ቀን ቢሮ ስትበሰጫጭ ስላያት ትንሽም ቢሆን አዘኖላታል። ያሳዘነችው ፤ ነገሩ የአሳ ጎርጓሪ ነገር ...ስለ ሆኖባት ነው። እነዚያን ባሏ እሷን ያሰለለበት ፎቶ ግራፎች ጉዳይ ልታዋራው ነበር የመጣችው።
ቅሌቷን በተለያዩ ማስተዛዘኛዎች እያዋዛች ነገረችው። ያቺ የተረገመች ቀን እና ያንን የተረገመ ወጣት፤ እንዴት ወደማትፈልገው ቅሌት እንዳስገቧት እየተቁለጨለጨች አስረዳችው። ለትዳሯ ምን ያህል ክብር እንደነበራትም አብራራችለት። ያም ሆኖ ግን፤ ከባሏ ትኩረት ስታጣ ወደ ቅሌት መግባቷን ምክንያታዊ፣ ለማስመሰል እየሞከረች አወራችለት። አንዱንም ቢሆን አላመነበትም። ቢያምንበትም ግን ምንም ሊያደርግ እንደማይችል ልቡ ያውቀዋል።
"ሚስተር ዮናታን ፣ እባክህ ፋይሎቹን አጥፋልኝና የምትፈልገውን ልክፈል ... እባክህን !" ስትል በውስጡ ሲፈራው የነበረውን ጥያቄ በማንሳት በጣም ለመነችው።
ትንሽ ጊዜ ስጪኝና ፣ ልረዳሽ የምችለው ነገር ካለ አሳውቅሻለሁ ...
ሲላት ምን እያላት እንደሆነ ግን በፍፁም አላስተዋለውም። ብቻ ልመናዋን እና ማስተዛዘኗን አቁማ እንድትወጣለት ነበር። አመስግና፣ ተሰናብታው ወጣች።
* * *
ዮናታን የክፍሉን ማሞቂያ ከፍቶ ፣ አልጋው ላይ ጋደም አለና ፤ ለስለስ ያለ ሙዚቃውን ከፍቶ ትዝታውን መኮምኮም ጀመረ። ከቴሌቪዥኑ ክርክር ግን፤ ራሱን ማላቀቅ አልቻለም። ኢትዮጵያ ውስጥ በሥራ ሳይሆን በፖለቲካ ተከልሎ መኖር የሚፈልግ ሰው ቁጥር ስፍር የለውም።
ሁሉም ፖለቲከኛ፣ ሁሉም ተንታኝ፣ ሁሉም መሪ፤ መሆን ይፈልጋል። ይህ እንዴት ይቻላል ?
ብሎ መልስ የሌለውን ጥያቄ ጠየቀ።መልስ የሌለው ጥያቄ፤ ማንም ሊመልሰው አይችልም። ፖለቲካ ቫይረስ ስለሆነ ፤ በቀላሉ ተጋብቶበት በቀላሉ አልለቅህ ብሎታል።
* * *
እንቅልፍ እስኪወስደው ሙዚቃውን እያደመጠ ፒዲኤፍ ክራውለው ሶፍትዌሯን ከፈተና እንደለመደው መጎርጎር ጀመረ። በአንድ ወቅት ፣ ዮናታን ሶፍት ኮፒ መፅሐፍቶችን የምትሰበስብ ይህችን ፒዲኤፍ ክራውለው ሶፍትዌርን በመስራት ፤ በርካታ መፅሐፍት ለመሰብሰብም ተጠቅሞባታል። ያኔ ኢትዮጵያ ተማሪ በነበረ ጊዜ ፤ የነበረውን የመፅሐፍት እጥረት ትዝ ሲለው ተበሳጭቶ ነበር ሶፍትዌሯን የሰራት። ዮናታን ተማሪ ሳለ መፅሐፍት ማግኘት ብርቅ ነበር። ዛሬ ግን ዮናታን የሚነበብ መፅሐፍ ሳይሆን፤ የሚያነብበት ጊዜ ነው ያጣው።
የትላንትን እጥረት በዛሬ መትረፍረፍ የተዋጋ ይመስል ፤ በትርፍ ጊዜው፣ በዛሬው ብቸኝነቱን ለመርሳት ሶፍት ኮፒ መፅሐፍቶችን ይሰበስባል። ፒዲኤፍ ክራውለው ሶፍትዌር በአሜሪካ ህግ፥ ህገ-ወጥ ብትሆንም፤ ውጤታማ የመፅሐፍት መሰብሰቢያ ሶፍትዌር ነች። የሰበሰባቸውን ፋይሎች መፅሐፍ የሆኑትንና ፣ ያልሆኑትን ከለየና በየምድባቸው ካስተካከለ ባኋል ፤ በሀርድ ዲስክ ያስቀምጣቸዋል። በእርግጥ ይህ ተግባሩ በህግ ቢደረስበት ፤ ምን ሊያስከትልበት እንደሚችል ቢያውቀውም፤ ማሰብ ግን አይፈልግም። ባለፉት አራት ዓመታት ብቻ ከአራት ሚሊዮን በላይ መፅሐፍቶችን ሰብስቧል።
* * *
ሶፍትዌሯ ስትሮጥ ፣ ዮናታን አልጋው ላይ ጋደም ብሎ የሚያዳምጠው ሙዚቃ ብዙ ተጫውቷል። በሙዚቃው ተመስጦ አንዴ ስለ እናቱ አንዴ ስለእናት አገሩ እያፈራረቀ ያስባል። የእናቴ ውለታ የአገሬ ትዝታ ባለሁበት ቦታ ...
የሚለው ግጥም ጋር ሲደርስ ፣ የእናቱ ትዝታ ጠንከር ስላለበት ፤ ስልኩን አንስቶ ደወለ። ስልኩ ይጠራል ግን የሚያነሳ የለም። ደግሞ ደጋግሞ ደወለ ፤ የሚያነሳ ግን የለም። የዮናታን እናት ህጋዊ ስማቸው ወ/ሮ ማንጠግቦሽ አዳፍሬ ይባላሉ። ተጨዋችና ሰው ወዳድ የሆኑ ሰው ናቸው።
ወ/ሮ ማንጠግቦሽ እነ ዮናታንን ለማሳደግ ያላዩት ፍዳ የለም። ኑሮ በደከመና ፣ በፈጋ ቢሆን ኖሮ፤ የእሳቸውን ያህል አሳሩን የበላ ሰው በፍፁም አይገኝም። በእርግጥ ከዚህ ሁሉ የኑሮ ፍጋት ገንዘብ ባያገኙምበትም ተግባቢነትና ተጫዋችነት ተክነውበታል።
ወ/ሮ ማንጠግቦሽ ጋር ለመጫወትና ለመግባባት ሰው ብቻ መሆን በቂ ነው። ብሔር፣ ኅይማኖት፣ ዕድሜና ፆታ አይገዳቸውም። ጫወታቸው በጣም ደስ ስለሚል ሰው ሁሉ እንዲያጫውቱትና እንዲያስቁት ይፈልጋል። ችግሩ አንዴ ጨዋታ ከጀመሩ፤ ቤታቸው ይረሳሉ። አንዳንድ የሰፈር ሰው ይህንን ተጫዋችነታቸውን ስለማይወዱት ፤ ማንጠግቦሽ ጨዋታ ስለምታበዛ ነው ትዳሯን በጊዜ ፈታ ዘመኗን ሁሉ በብቸኝነት ስትሰቃይ ነው የኖረችው።
ሲሉ ያሟቸዋል። በእርግጥ እውነታው እንኳን ያ አልነበረም። ወ/ሮ ማንጠግቦሽ እነ ዮናታን ህፃን እያሉ ነበር ትዳራቸው የፈረሰባቸው። ከዚያን ወዲህ ትዳር ቢፈልጉም ሁለቱን ልጆች እያየ የሚጠጋ ደፋር በመጥፋቱና ፤ በኑሮም የሚደግፋቸውም ባለመገኘቱ፤ ሁሉን እርግፍ አድርገው ትተው፤ አዲስ አበባ ገቡ እና ፍዳቸውን አይተው ዮናታንና ወንድም ሚልኪያስን አሳደጉ።
* * *
ወ/ሮ ማንጠግቦሽ ስለ አቻ ጋብቻ ያለኝ አቋም ግልፅ ነው።
ብለው ነው የሚያምኑት። ጥያቄው አቻ ምንድነው የሚለው እንደሆነ ግን ልብ አይሉትም። በእርሳቸው እምነት ፤ ሰው ዘሩ የሚመዘዘው ከአንድ ሀረግ ነው ይባል እንጂ ፤ ሰው ሲጋባ ዘር ግንዱን አይቶና ትውልዱን ቆጥሮ መሆን አለበት። ከዚህም የተነሳ ያችን አዲስ አበባ የምትኖረውና ሜሮን አባተ የምትባል፣ ትምህርት ቤት ሳለ የተዋወቃትን የዮናታን ሴት ጓደኛ ፣ ለልጃቸው የጋብቻ አቻ እንዳልሆነች ነው የሚሰማቸው። ስለሷ ምንም ነገር እንዲወራላቸው አይፈልጉም። እርሱም ቢሆን ወደፊት ሊያገባት የሚፈልጋት እንደሆነች አይነግራቸውም። ልባቸው ግን በደንብ አሳምሮ ያውቀዋል ፤ አንድ ቀን ዮናታን ሜሮን አግብቶ ፣